በዘንድሮ የትምህርት ዓመት በዩኒቨርስቲዎች በተቀሰቀሱ ግጭቶች 12 ተማሪዎች ለሞት ተዳርገዋል – ሪፖርት

እየተገባደደ ባለው 2012 ዓ.ም. በ28 ዩኒቨርስቲዎች በተቀሰቀሱ ግጭቶች 12 ተማሪዎች ለሞት መዳረጋቸውን የመብቶች እና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል (ካርድ) የተባለው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አስታወቀ። ድርጅቱ ዛሬ ባወጣው ጥቅል ዓመታዊ መግለጫ እንደገለጸው በዚህ ዓመት የትምህርት በተከሰቱ ግጭቶች ብቻ ቢያንስ በ58 ተማሪዎች ላይ ቀላል እና ከባድ ጉዳት ደርሷል። 

ካርድ “የዩኒቨርስቲ ውስጥ ግጭቶች” በሚል ርዕስ ያዘጋጀው ባለ 54 ገጽ ሪፖርት ከመስከረም 2012 ዓ.ም ጀምሮ በኮቪድ 19 ወረርሽኝ ምክንያት ትምህርት ቤቶች እስከተዘጉበት ጊዜ ድረስ በዩኒቨርቲዎች የተከሰቱ ግጭቶችን ዳስሷል። ሪፖርቱ በዩኒቨርስቲዎች ውስጥ በተማሪዎች መካከል የሚከሰቱ ግጭቶች ከዓመት ወደ ዓመት እያሻቀቡ መጥተዋል ብሏል። 

የዘንድሮውን የትምህርት ዓመት በተመለከተ “ዓመቱ በግጭቶች ምክንያት ትምህርት የተስተጓጎለበትና የተማሪዎች ደኅንነት አደጋ ላይ የወደቀበት ሆኖ አልፏል” ሲሉ ካርድ በሪፖርቱ ግምገማውን አስፍሯል። ድርጅቱ ባደረጋቸው ዳሰሳዎች እና ውይይቶች፤ የችግሮቹ ምንጮች ከትምህርት ስርዓቱ፣ ከአስተዳደር ሁኔታዎች እና ከአገሪቱ የፖለቲካ እውነታ ጋር የተያያዘ መሆኑን የሚያመለክቱ መረጃዎችን ማግኘቱን ገልጿል።

በጥቅምት ወር መጨረሻ በወልዲያ ዩኒቨርስቲ በተከሰተ ግጭት የሁለት ተማሪዎች ህይወት ማለፉን ተከትሎ በቀጣዩ ወር በ16 ዩኒቨርስቲዎች ተመሳሳይ ክስተቶች መፈጠራቸውን ካርድ በማሳያነት ጠቅሷል። “ግጭቶቹ የብሔር መልክ ያላቸው ሲሆን፣ ማኅበራዊ ሚዲያዎች በሐሰተኛ መረጃዎች ግጭቶቹን የማቀጣጠል ሚና እንደተጫወቱም ተስተውሏል” ሲል በዩኒቨርስቲዎቹ የነበሩ ሁከቶች መነሻ ምክንያቶችን አመላክቷል። 

የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን ለጉዳት የሚዳርጉ ግጭቶች መንስኤ ምንድነው ተብሎ ሲጠየቅ አብዛኛውን ጊዜ “በተጨባጭ ይህ ነው የሚል ምላሽ አይገኝላቸውም” የሚለው ካርድ፤ ካደረገው ዳሰሳ በመነሳት የደረሰበትን ድምዳሜ በሪፖርቱ አስቀምጧል። እንደ ድርጅቱ ገለጻ “የግጭቶቹ መንስዔ ብዙ ጊዜ የግል ወይም የሌላ ዩኒቨርሲቲ ግጭት ሆኖ፣ የሚቀጣጠለው ግን የብሔር ፀብ በመሆን ነው።” 

በዩኒቨርስቲዎች ያሉ አለመረጋጋቶች “በብዙዎች እንደሚገመቱት ተማሪዎች ብቻ የሚሳተፉበት አይደለም” ሲል ካርድ በሪፖርቱ አመልክቷል። “የዩኒቨርሲቲው መምህራኖች፣ የአስተዳደር ሠራተኞች፣ ፕሮክተሮች እናም ሌሎች የችግሩ አባባሽ ይሆናሉ ተብለው የማይገመቱ አካላት እጃቸውን እንዳለበት በአንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች መረጋገጡ አሁንም ጉዳዩ የተማሪዎች ብቻ ነው ብለን መደምደም እንደሌለብን የሚጠቁም ነው” ሲልም አጽንኦት ሰጥቷል። 

“የዩኒቨርሲቲው መምህራኖች፣ የአስተዳደር ሠራተኞች፣ ፕሮክተሮች እናም ሌሎች የችግሩ አባባሽ ይሆናሉ ተብለው የማይገመቱ አካላት እጃቸውን እንዳለበት በአንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች መረጋገጡ አሁንም ጉዳዩ የተማሪዎች ብቻ ነው ብለን መደምደም እንደሌለብን የሚጠቁም ነው”

የመብቶች እና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል

ግጭት የተከተሰባቸው ዩኒቨርስቲዎች በወሰዱት እርምጃ በርካታ ተማሪዎችና ሠራተኞች ከትምህርት እና የሥራ ገበታቸው መታገዳቸውን የሚጠቅሰው ካርድ፤ በተጠርጣሪ ተማሪዎች እና ሰራተኞች መካከል ያለውን ትስስር ይበልጥ ለመገንዘብ “ግጭቶቹን በሚገባ ማጥናት ያስፈልጋል” ብሏል። ድርጀቱ ሪፖርቱን ሲያዘጋጅም “ለተጨማሪ ምርመራ እና የመከላከል ሥራ እንዲያግዝ” በማሰብ እንደሆነም አመልክቷል።   

ጥቅል ዓመታዊ መግለጫው “ጉድለቶች” እንዳሉበት ያመነው ካርድ፤ በአቅም ውሱንነት ምክንያት ድርጅቱ መረጃዎቹን ያሰባሰበው በቦታው በመገኘት ሳይሆን ከይፋዊ መግለጫዎች እና የመገናኛ ብዙሃን ዘገባዎች መሆኑን አብራርቷል። “መግለጫውን በማዘጋጀት ሂደት፤ በተለያዩ አካላት ለዜና አውታሮች የተሰጡ አስተያየቶች እና ምስክርነቶች አንዳንዴ እርስ በርሳቸው የሚጋጩ በመሆናቸው እውነቱ የትኛው እንደሆነ መናገር አስቸጋሪ አድርጎታል” በማለት የገጠመውን ተግዳሮት በሪፖርቱ ጠቅሷል። ሆኖም “ይህም እንደ ችግሩ አካልነት ሊታይ ይገባል” ብሏል። 

ካርድ በሪፖርቱ ማጠቃለያ በሰጠው ጥቆማ “ዩኒቨርሲቲዎችን በፌደራል ፖሊሶች እንዲጠበቁ ማድረግ ጊዜያዊ መረጋጋትን እንጂ ዘላቂ ሰላምን ሊያረጋግጥ አይችልም” ሲል መክሯል። ጥፋቶች ከተከሰቱ በኋላ ተመጣጣኝ እርምጃዎች እና እርምቶች አለመውሰዳቸውንም እንደ አንድ ችግር አንስቷል። 

“በሕግ አግባብ ሊፈቱ የሚገባቸው ወንጀሎች በዕርቅ ስም እንዲታለፉ እና በተማሪዎች መካከል የቂም በቀል ስሜት እና ቁጭት እንዲዳብር መንስኤ ሆነዋል” ያለው ካርድ፤ “የእርምት እርምጃዎቹ ተመጣጣኝ መሆን ይገባቸዋል” ሲል መደረግ አለበት ያለውን ጠቁሟል። (በተስፋለም ወልደየስ – ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)