በቤርሳቤህ ገብረ
መንግስታዊው የቴሌኮም አገልግሎቶች አቅራቢ የሆነው ኢትዮ ቴሌኮም፤ “ዘመን ገበያ” የተሰኘ ሀገር አቀፍ “የዲጂታል ገበያ” መጀመሩን አስታወቀ። የዲጂታል ገበያው በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ አምራች እና ነጋዴዎችን፣ ገዢዎችን እና የሎጅስቲክስ ተቋማትን “በቀላሉ ለማገናኘት የሚያስችል ነው”ተብሎለታል።
ኩባንያው የዲጂታል ገበያውን ይፋ ያደረገው፤ ዛሬ ሐሙስ ሚያዝያ 30፣2017 ዓ.ም. አዲስ አበባ በሚገኘው የሳይንስ ሙዚየም ባዘጋጀው መርሃግብር ላይ ነው። በመርሃ ግብሩ ላይ ገለጻ ያደረጉት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ፤ የዲጂታል ገበያው የተጀመረው በ40 ተቋማት እና በ14 የምርት አይነቶች መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮ ቴሌኮም ያቀረበውን ጥሪ ተከትሎ የዲጂታል ገበያውን ከተቀላቀሉ ተቋማት ውስጥ ማለዳ ፎም፣ ሸዋ ሾፒንግ፣ ኦል ማርት እና አፍሪ ሀርባል የተሰኙት ድርጅቶች ተጠቃሽ ናቸው። የዲጂታል ገበያው በቴሌብር “ሱፐር አፕ” ስር ባለ ትንሽ መተግበሪያ (mini app) ውስጥ የሚገኝ ሲሆን፤ ተቋማቱ ምርት እና አገልግሎታቸውን የሚያቀርቡት በየራሳቸው “ቨርችዋል ስቶር” ነው።
በዲጂታል ገበያው መገልገል የሚፈልጉ የኢትዮ ቴሌኮም ደንበኞች፤ የመረጡትን እቃ ለመግዛት አሊያም አገልግሎት ለማግኘት ክፍያ የሚፈጽሙበት የቴሌ ብር አካውንት ያስፈልጋቸዋል። ደንበኞች ለሚገዙት ዕቃ ወይም ምርት የሚፈጽሙት ክፍያ፤ በአድራሻቸው የሚደርስበትን የማጓጓዣ ወጪ ይጨምራል።
አምራቾች እና ነጋዴዎች ከኢትዮ ቴሌኮም ክፍያውን የሚያገኙት፤ የተገዛው እቃ ደንበኞች እጅ ከገባ በኋላ እንደሆነ በዛሬው መርሃ ግብር ላይ ተገልጿል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)
[በዚህ ዘገባ ላይ ከቆይታ በኋላ ተጨማሪ መረጃ ታክሎበታል]