በግለሰቦች፣ በብሔር ብሔረሰቦች እና ህዝቦች መካከል “ስጋት፣ ግጭትን፣ ጥርጣሬን እና አለመተማመንን የሚፈጥር ድርጊት ፈጽሟል” ያለውን የፖለቲካ ፓርቲ፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከምዝገባ እንዲሰርዝ ስልጣን የሚሰጥ የአዋጅ ማሻሻያ ለፓርላማ ቀረበ። ቦርዱ የሌላ ፖለቲካ ፓርቲን “ህጋዊ እና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ያደናቀፈ” የፖለቲካ ፓርቲ ላይ ተመሳሳይ እርምጃ የመውሰድ ስልጣንም በአዋጅ ማሻሻያው ተሰጥቶታል።
ላለፉት አምስት ዓመታት በስራ ላይ የቆየውን “የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ እና የምርጫ ስነምግባር አዋጅ” ያሻሻለው የህግ ረቂቅ ለፓርላማ የቀረበው፤ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ አርብ ሰኔ 27፤ 2017 ባካሄደው ልዩ ስብሰባ ላይ ነው። ለዕረፍት ሊበተኑ ጥቂት ቀናት የቀራቸው የፓርላማ አባላት፤ በአዋጅ ማሻሻያው ላይ መታየት ያለባቸውን ጉዳዮች በጥቂቱ ካቀረቡ በኋላ በዝርዝር እንዲታይ ለምክር ቤቱ የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መርተውታል።
ያለምንም ተቃውሞ እና ድምጸ ተዐቅቦ ለቋሚ ኮሚቴ የተመራው ይህ የአዋጅ ማሻሻያ ከተዘጋጀባቸው ምክንያቶች አንዱ፤ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስፈጸመው ጠቅላላ ምርጫ ወቅት የተስተዋሉ “የህግ ክፍተቶች” እንደሆነ የህግ ረቂቁን ለማብራራት በቀረበ ሰነድ ላይ ተጠቅሷል። በተመሳሳይ መልኩ “የህግ ክፍተቶች” በፖለቲካ ፓርቲ አስተዳደር ስራዎች ላይ እንዳሉ ያመለከተው ሰነዱ፤ ይህንኑ ለመቅረፍ የአዋጅ ማሻሻያው መዘጋጀቱን ይገልጻል።

ከዚህ በተጨማሪም በምርጫ ተሳታፊ የሚሆኑ ባለድርሻ አካላት፤ ምርጫውን “ሰላማዊ እና ፍትሃዊ በማድረግ ከማስፈጸም አንጻር” ያላቸውን “መብት እና ግዴታ” ለመደንገግ የአዋጅ ማሻሻያው እንደተዘጋጀ በማብራሪያው ላይ ሰፍሯል። ዛሬ ለፓርላማ የቀረበው የህግ ረቂቅ ካካተታቸው ማሻሻያዎች መካከል፤ የፖለቲካ ፓርቲዎችን “መታገድ፣ መሰረዝ እና መፍረስ” የሚመለከተው ክፍል ይገኝበታል።
በነባሩ አዋጅ ላይ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ ከምዝገባ የሚሰረዘው በሶስት ምክንያቶች እንደሆነ ተቀምጧል። የመጀመሪያው ምክንያት አንድ የፖለቲካ ፓርቲ “በመተዳደሪያ ደንቡ መሰረት በራሱ ፈቃድ ከምዝገባ እንዲሰረዝ ሲጠይቅ” ሁለተኛው ደግሞ በአዋጁ መሰረት “የፖለቲካ ፓርቲው እንዲሰረዝ ፍርድ ቤት ውሳኔ ሲሰጥ ነው”።
እንደ ፍርድ ቤት ሁሉ ብሔራዊው ምርጫ ቦርድም፤ አዋጁን መሰረት አድርጎ በሚያሳልፈው ውሳኔ የአንድ የፖለቲካ ፓርቲ ምዝገባ መሰረዝ እንደሚችል አሁን በስራ ላይ ባለው አዋጅ ተደንግጓል። ምርጫ ቦርድ ይህን ውሳኔ የሚያሳልፍባቸው ተብለው በነባሩ አዋጁ ከሰፈሩ ስድስት ጉዳዮች ሌላ አዲሱ የአዋጅ ማሻሻያ አምስት ተጨማሪ ምክንያቶችን ዘርዝሯል።

አንድን የፖለቲካ ፓርቲ በምርጫ ቦርድ ሊያሰርዙት ከሚችሉ ምክንያቶች አንዱ “በአዋጅ የተቀመጠው ዝቅተኛ የፖለቲካ ፓርቲ መስራች አባላት ቁጥር መጓደል” ነው። በጥቅምት 2012 ዓ.ም በጸደቀው አዋጅ መሰረት፤ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ በሀገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲነት የሚመሰረተው 10 ሺህ መስራች አባላት ሲኖሩት ነው።
ይኸው አዋጅ የክልል ፖለቲካ ፓርቲ ለመመስረት የሚያስቀምጠው ዝቅተኛ የመስራቾች ቁጥር አራት ሺህ ነው። የፖለቲካ ፓርቲው “ዝቅተኛ የመስራች አባላት የተጓደሉበት እንደሆነ” እና በሁለት ወራት ጊዜ ውስጥ እንዲያስተካክል በቦርዱ ተጠይቆ “ሳያስተካክል የቀረ እንደሆነ” ከምዝገባ እንደሚሰርዝ በአዋጅ ማሻሻያው ላይ ተቀምጧል።
አንድ የፖለቲካ ፓርቲ ለምርጫ ቦርድ በሚያቀርበው የሂሳብ ኦዲት ሪፖርት ላይ “ጉልህ የሆነ” የሂሳብ ጉድለት ወይም “ምዝበራ ስለመፈጸሙ ከተረጋገጠ” ምዝገባው እንደሚሰረዝ በህግ ረቂቁ ላይ ሰፍሯል። በነባሩ አዋጅ ላይ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ “ለቦርዱ ማቅረብ ያለበትን ዓመታዊ የስራ፣ የሂሳብ ወይም ሌሎች ሪፖርቶች በአዋጁ በተወሰነው ጊዜ ሳያቀርብ ሲቀር እና ይህንኑ በ30 ቀናት ውስጥ እንዲያቀርብ በቦርዱ ተጠይቆ ያለ በቂ ምክንያት ሳያቀርብ የቀረ እንደሆነ” በተመሳሳይ መልኩ ምዝገባው እንደሚሰረዝ ተደንግጓል።

በአዲሱ የአዋጅ ማሻሻያ የተካተተው ሌላኛው የምዝገባ ማሰረዢያ ምክንያትም እንዲሁ ምርጫ ቦርድ በሚያስቀምጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ “ከድርጊቱ እንዲቆጠብ” ወይም “ማስተካከያ እንዲያደርግ” ያስገድዳል። የፖለቲካ ፓርቲው ይህን እንዲያደርግ የሚገደደው “በግለሰቦች፣ በብሔር ብሔረሰቦች እና ህዝቦች መካከል ስጋት፣ ግጭትን፣ ጥርጣሬን እና አለመተማመንን የሚፈጥር ድርጊት የፈጸመ” እንደሆነ ነው።
የፖለቲካ ፓርቲው ይህን ድርጊት መፈጸሙን የሚወስነው ምርጫ ቦርድ፤ “ እንደ ጉዳዩ ክብደት እያየ” የጊዜ ገደብ እንደሚያስቀምጥ በህግ ረቂቁ ላይ ተመልክቷል። ቦርዱ “የሌላ ፖለቲካ ፓርቲን ህጋዊ እና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ያደናቀፈ” የፖለቲካ ፓርቲ ላይም “ከድርጊቱ እንዲቆጠብ” ወይም “ማስተካከያ እንዲያደርግ” በተመሳሳይ መልኩ የጊዜ ገደብ እንደሚሰጥ በአዋጅ ማሻሻያው ላይ ተቀምጧል።
ምርጫ ቦርድ የሚሰጠው የጊዜ ገደብ “አባላትን ከፍላጎታቸው ውጪ በኃይል ወይም በማስገደድ የመለመሉ” የፖለቲካ ፓርቲዎች ላይም ተግባራዊ የሚደረግ ነው። የፖለቲካ ፓርቲው ምርጫ ቦርድ “እንደ ጉዳዩ ክብደት እየታየ” በሚያስቀምጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ከድርጊቱ ያልተቆጠበ” እንደሆነ ከምዝገባ እንደሚሰረዝ አዲሱ አዋጅ ይደነግጋል።

በዚሁ የአዋጅ ማሻሻያ ላይ ከዚህ ቀደም ያልነበረ “የፖለቲካ ፓርቲን ማገድ” የሚመለከት አንቀጽ ተጨምሯል። የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚታገዱት በነባሩ እና በማሻሻያ አዋጁ ላይ የተቀመጡ ጥሰቶችን መፈጸማቸው ሲረጋገጥ እንደሆነ ለፓርላማ በቀረበው የህግ ረቂቅ ላይ ተመልክቷል።
“ምርጫ ቦርድ በአዋጁ በተመለከተው አግባብ ጥሰት መፈጸሙ የተረጋገጠ የፖለቲካ ፓርቲን ከምዝገባ ከመሰረዙ በፊት፤ የጥሰቱን አይነት፣ ክብደት እና ሌሎች ሁኔታዎች ከግምት በማስገባት ከአምስት ዓመት ላልበለጠ ጊዜ ታግዶ እንዲቆይ ሊወስን ይችላል” ይላል አዲሱ የአዋጅ ማሻሻያ። ሆኖም ቦርዱ የእገዳ ውሳኔ ከማሳለፉ በፊት “የፖለቲካ ፓርቲው መከላከያውን አቅርቦ እንዲሰማ ማድረግ አለበት” ሲልም ያክላል።
ቦርዱ ያሳለፈውን የእገዳ ውሳኔ የሚቃወም የፖለቲካ ፓርቲ፤ ውሳኔው በደረሰው በሰላሳ ቀናት ውስጥ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ ማቅረብ እንደሚችል በህግ ረቂቁ ላይ ተቀምጧል። የፖለቲካ ፓርቲው አቤቱታ ተቀባይነት የማያገኝ ከሆነ ግን “እገዳው ጸንቶ በሚቆይበት ጊዜ ማንኛውንም አይነት የፖለቲካ እንቅስቃሴ ማድረግ እና በየትኛውም ደረጃ በሚደረግ ምርጫ ላይ መሳተፍ እንደማይችል” በአዋጅ ማሻሻያው ላይ ተደንግጓል።

ከዚህ በተጨማሪ የፖለቲካ ፓርቲው በእገዳ ጊዜው “በጋራ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምክር ቤት ውስጥ መሳተፍ እንደማይችል” እና “ከመንግስት የሚገኝ ድጋፍ ተጠቃሚ እንደማይሆን” በህግ ረቂቁ ላይ ሰፍሯል። የእግድ ውሳኔ የተላለፈበት አንድ የፖለቲካ ፓርቲ “ሌላ ጥፋት ከፈጸመ”፤ የእገዳ ጊዜው ከማብቃቱ በፊት ምርጫ ቦርድ “ተገቢውን ህጋዊ እርምጃ ሊወስድ እንደሚችል” በአዋጅ ማሻሻያው ላይ ተካትቷል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)































